ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, March 16, 2024

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።



Monday, February 19, 2024

የኢትዮጵያ ድንቅ መስተንግዶ ዳግም የተመሰከረበት የአፍሪካ ኅብረት 37ኛ የመሪዎች ጉብዔ ዛሬ ሰኞ ተጠናቀቀ።ኢትዮጵያን የሚመጥነው የኢትዮጵያ መስተንግዶ በቪድዮ።

በእዚህ ሊንክ ስር ፡ 
  • መሪዎቹ የተወያዩባቸው አራቱ አጀንዳዎች ምን ነበሩ? (አጀንዳዎቹ በአጭሩ ተዘርዝረዋል)
  • እድሳቱ በቅርቡ የተጠናቀቀው ብሔራዊ ቤተመንግስት የተደረገው የራት ግብዣ የእንግዶች አቀባባል (ቪድዮ ይመልከቱ)
  • የአዲስ አበባ ከተማ ቸርችል ጎዳና የሰሞኑ የምሽት ገጽታ እንደወረደ (ቪድዮ ይመልከቱ)
=============

የአፍሪካ ኅብረት 37ኛ የመሪዎች ጉባዔ አራቱ አጀንዳዎች፡ 

1. የትምህርት ተደራሽነትና ጥራት የዘንድሮ የፈረንጆች ዓመት የትምህርት ዘመን ተብሎ መሰየሙን ተከትሎ የኅብረቱ ጉባኤ በአህጉሪቱ የትምህርት ተደራሽነትና ጥራት ለማረጋገጥ ሊሰሩ በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ መክሯል። የመንግሥታቱ ድርጅት መረጃ እንደሚያሳየው፤ በአፍሪካ በተለይም ከሰሃራ በታች በሚገኘው የአህጉሪቱ ቀጣና በዓለም የትምህርት ተደራሽነት ካልተረጋገጠበት አከባቢ ቀዳሚ ነው። ለአብነትም አጠቃላይ በአህጉሪቱ ከሚገኙ እድሜያቸው ከ15 እስከ 17 የመሆኑ ታዳጊ ወጣቶች 60 በመቶ የሚሆኑት ከትምህርት ገበታ ውጪ ናቸው። ትምህርታቸውን የሚያቋርጡ ታዳጊዎች ቁጥርም አጅግ ከፍተኛ ነው። ብቂ መምህራን የማሰማራት እንዲሁም አህጉሪቱን ለመለወጥ የሚያስችሉ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፉ የተግባር ትምህርቶች ተደራሽነትም ከሚፈለገው በታቸ ነው።

2. አህጉራዊ ምጣኔ ኃብታዊ ትስስር የአፍሪካን ከውጭ የፋይናንስ ጥገኝነት ለማላቀቅና ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊና ምጣኔ ኃብታው ችግሮችን ለመቅረፍ የውስጥ አቅምን አሟጦ መጠቀም በተመለከተ ውይይት ተደርጓል። በዚህ ረገድ በተለይም ትልቅ ግምት የተሰጠው አሁን በሙከራ ደረጃ ላይ የሚገኘው አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የእስካሁኑ ሂደትና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ምክክር ተደርጓል። ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ በአህጉሪቱ 30 ሚለየን ሰዎችን ከድኅነት የማውጣት እንዲሁም እንደ አውሮፓውያኑ አቆጠጣር በ2035 በአፍሪካ ገቢን በ7 በመቶ እንደሚጨምር ተስፋ የተጣለበት ይኸው የንግድ ቀጣና በፍጥነት ወደ ሥራ እንዲገባ አገራት ከታሪፍና ከሌሎች የንግድ ሂደት ጋር ያሉ ውስብስብ አሰራሮችን እንዲያስወግዱ አቅጣጫ ላይ መክሯል።

3. አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላት ሥፍራ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ተቋማት ያላትን ውክልና ተገቢውን ሥፍራ እንድትይዝ በተለይም በመንግሥታቱ ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ያላትን ውክልና በተመለከተ ለበርካታ ዓመታት ስትጠይቅ ቆይታለች። ይህንን ጨምሮ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማትም የአፍሪካን ፍላጎት ያገናዘበ ቁመና ሊኖረው ይገባል የሚለውም አጀንዳ የዘንድሮው ጉባኤ አጀንዳ ነበር ። አፍሪካ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ የባለብዙ ወገን መድረኮች ጋር በተለይም አሁን አፍሪካ የቡድን 20 አገራት አባል መሆኗን ተከትሎ እንዲሁም ተጽዕኖ ፈጣሪነቱ እየገነነ ከመጣው ከብሪክስ ጋር ባላትና ሊኖራት በሚችለው ግንኙነት ዙሪያም ምክክር ተደርጎበታል። በተለይም አፍሪካ እንደ ተጨማሪ የቡድን 20 አባልነቷ፤ ምን ይዛ ልትሄድና ልታመጣ ትችላለች እንዲሁም አባልነቷን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ለበርካታ ዓመታት ተፈልጎ የታጣውን ውክልና ለመካስ ወይም የአህጉሪቱን ድምጽ ይበልጥ ለማሰማት በሚቻልባቸው ምቹ ሁኔታዎች ዙሪያ ምክክር ተደርጓል።

4. የሠላምና ደኅንነት ተግዳሮቶችና መፍትሄያቸው የመሪዎቹ ጉባኤ ዘንድሮም በአፍሪካ የጸጥታ ችግሮች ዙርያ ምክክር አድርጓል። አህጉሪቱን ከድኅረ -ነጻነት በኋላ በእጅጉ እየፈተኑ ከሚገኙ ከነገረ ፖለቲካዊ ጉዳዮች መካከል ቀዳሚውን ሥፍራየሚይዘው የጸጥታ መደፍረስ ነው። ሽብርተኝነት፣ ኢ-ሕገ-መንግሥታዊ የሥልጣን መቆናጠጥ፣ ግጭቶችና ከምርጫ ጋር የተያያዙ የፖለቲካ አለመረጋጋት እና ሌሎች መሰል ቸግሮች አሁንም ለአፍሪካ ፈተና ሆነው ቀጥለዋል። እነዚህ የፖለቲካ ቀውሶች አህጉሪቱ በየትኛውም ማኅበራዊና ምጣኔ ኃብታዊ መስክ ወደፊት ፈቅ እንዳትል ካደረጓት ምክንያቶ ዋነኛው መሆኑን ነው የተለያዩ ጥናቶች የሚያሳዩት። እነዚህን ግጭቶች ባሉበት ለማቆምና ሌሎችም በቀጣይ እንዳይከሰቱ በተለይም የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል (ውይይት) ብቸኛ አማራጭ ለማድረግ ኅብረቱ ከዚህ ቀደም የጀመራቸውን ሥራዎችና ሌሎች ተግባራትን ለማጠናከር በሚያስቸሉ ጉዳዮች ላይ መሪዎቹ ውይይት አድርገዋል፣የመፍትሄ አቅጣጫዎችም ስብሰባው አስቀምጧል።

እድሳቱ በቅርቡ የተጠናቀቀው ብሔራዊ ቤተመንግስት የተደረገው የራት ግብዣ የእንግዶች አቀባባል (ቪድዮ)


የአዲስ አበባ ከተማ ቸርችል ጎዳና የሰሞኑ የምሽት ገጽታ እንደወረደ (ቪድዮ)

ቪድዮው የሚጀምረው ከፒያሳ የአድዋ ድል መታሰብያ ሙዜም ዙርያ ነው።

ለጽሑፉና ቪድዮዎች ምንጮች ፡  

  • ENA
  • FBC
  • J.Walking Tour

Tuesday, January 23, 2024

ኢጃት ማን ነው? እንዴት ተመሰረተ? (ቪድዮ)

  • በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋኅዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምሕርትቤቶች ማደራጃ መምርያ ስር መዝግባ ዕውቅና ሰጥታዋለች።

  • ከክፍሎቹ ውስጥ ሦስቱ ፡የመዝሙር ክፍሉ ጃን ያሬድ  ሰሞኑን የአዕላፋት ዝማሬን ያቀረበው ሲሆን ሁለተኛው ጃን አጋፋሪ የዝግጅቶች አስተባብሪ ነው።ሦስተኛው ጃን ምኩራብ የሚድያ ክፍል ነው።

  • ኢጃት ሐያሁለት ፕሮጀክቶች ይዞ እየሰራ ነው።

  • ዋና ዓላማው በቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገለገልና የሚያገለግል ትውልድ ማፍራት ዓላማው የሆነውን የኢጃትን መልካም ሥራውን ለማጣጣል '' የክርስቶስ የሆኑትን ሊሳደብ አውሬው አፉን ከፈተ'' ተብሎ  በመጽሐፍ ላይ እንደተጻፈ በባሕር ማዶ ሆኖ በኢጃት ውጥን ስራዎች ላይ ሊሳለቅ የሞከረውን ከሰሞኑ ታዝበናል።

    በጎ ሥራ የሚሰራ ትውልድን ሁልጊዜ እናበረታታ!





Thursday, January 11, 2024

የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲን እጅግ ዘመናዊ በሆነ አቀራረብ የተዘጋጀው ዐውደ ርዕይ ዛሬ አዲስ አበባ በሳይንስ ሙዝየም ተከፍቷል (ቪድዮውን ይመልከቱ)

  • ዐውደ ርዕዩ ከንግስት ሳባ ጀምሮ ያለውን የኢትዮጵያ የውጪ ግንኙነት ያሳያል።
  • ኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር መስርያቤትን ስራ ካስጀመረች 116 ዓመታት እንደሆናት ዐውደ ርዕዩ ያሳያል።
  • በዛሬው መክፈቻ ስነስርዓት ላይ መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገሮች አምባሳደሮች ጨምሮ፣ከተልያየ ዓለም የመጡ የኢትዮጵያ ዲፕሎማቶች ተገኝተዋል።
  • ዐውደ ርዕዩ ከሁለት ሳምንታት በላይ ክፍት ሆኖ ይቆያል።በቀጣይ ቀናት በአዲስ አበባ ነዋሪ እና የዓለም ዓቀፍ ኮሚኒቲ ይጎበኛል ተብሎ ይጠበቃል።
  • በቅርቡ በአዲስ አበባ እንደሚደረግ የሚጠበቀው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ስብሰባ ላይ የሚገኙ የሀገራት መሪዎች፣የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችና ዓለም ዓቀፍ ጋዜጠኞች እንደሚጎበኙት ይጠበቃል።
ቀን ጥር 2፣2016 ዓም


Tuesday, December 5, 2023

በአማራ ክልል በሚደረገው ጦርነት ሳብያ የአማራ ክልል ህዝብ ላይ እየደረሰ ስላለው ሰቆቃ ያልሰማነው ከሰማነው ይበልጣል።


  • መከላከያ ክልሉን ለቆ ይውጣ የሚለው  አባባል የአማራ ክልል ጥያቄ ነው?
==========
ጉዳያችን ምጥን
=========

ወቅታዊው ሁኔታ

አሁን ባለው የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ትልቁ አጀንዳ በአማራ ክልል በታጣቂዎች እና በመከላከያ መሃከል እየተደረገ ያለው ጦርነት ነው።''ሁለት ሰዎች ሲጣሉ ችግሩ ቀላል ሊሆን ይችላል።ሁለት ሺህ ህዝብ ከሁለት ሺህ ህዝብ ጋር ሲጣላ ግን ጉዳዩ ጦርነት ነው '' የሚል አባባል አለ። በኢትዮጵያ አሁን እየሆነ ያለው ከተራ ግጭት ባለፈ ትርጉም የማይሰጥ የወንድማማቾች አሳዛኝ ጦርነት እየተደረገ ነው። ጦርነቱ ከመከላከያም ከታጣቂዎችም ሆነ ከሰላማዊው ህዝብ የሚወድቀው ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ የማትተካው ውድ የሰው ህይወት ነው። በአማራ ክልል አሁን ያለው ጦርነት መነሻ ምክንያት እና መፍትሄው በተመለከተ ከስድስት ወር በፊት ጉዳያችን ላይ ''የኦነግ/ኦህዴድ እና የህወሓት ጽንፈኝነት የአማራ ጽንፈኝነትን ወለደ። ኢትዮጵያን መልሰን ወደ አንደኛ ክ/ዘመን እንዳንከታት መንግስት የኃይል መንገድን ብቻ ከማሰብ ይልቅ ቀድሞ መከወን ያለበት ተግባር ላይ ያተኩር።'' በሚል ርዕስ ላይ ለመግለጽ ስለሞከርኩ እርሱን እዚህ ላይ ለመድገም አልፈልግም።ከእዚህ ይልቅ በወቅታዊው የአማራ ክልል ሁኔታ አንጻር ህዝቡ ያለበትን ነባራዊ ሁኔታ ዙርያ የተወሰኑ ነጥቦችን ላንሳ። እዚህ ላይ በአማራ ክልል ህዝብ ላይ በእዚህ ጦርነት ሳብያ እየደረሰ ያለውን ፈተና በውጭ የሚገኙ ዩቱበሮች ፈጽመው አያነሱትም።ዩቱበሮቹ ''ታጣቂዎች ይህንን ያዙ'' የሚል ዜና ላይ እንጂ በእዚህ ጦርነት የክልሉ ህዝብ የደረሰበት ማኅበራዊ፣ምጣኒያዊ ሐብታዊና ስነልቦናዊ ችግር ጥልቀት የሚናገር የለም።

አሁን በአማራ ክልል በሚደረገው ጦርነት ሳብያ የአማራ ክልል ህዝብ ላይ እየደረሰ ስላለው ሰቆቃ ያልሰማነው ከሰማነው ይበልጣል።

በአማራ ክልል ከተነሳው ጦርነት በኋላ የህዝብ ትራንስፖርት በአብዛኛው የክልሉ ከተማና ገጠር መሃል ግንኙነት ተቋርጧል፣ኢንተርኔት ለተወሰኑ ተቋማት ከመፈቀዱ በላይ ባብዛኛው ቦታ አይሰራም፣ከሁለት ሚልዮን ያላነሱ ህጻናት፣ታዳጊዎችና ወጣቶች ወደ ትምህርት ቤት እየሄዱ አይደለም።በጦርነቱ ሳብያ ከታጣቂዎችም ሆነ ከመንግስት ድሮን ጭምር የሚወነጨፉ አረሮች ሰላማዊ ህዝብንም ለሞት እየዳረገ ነው።የድሮን ጥቃቶቹን ተከትሎ ቢቢሲ ያነጋገራቸውን ጨምሮ የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን አረጋግጠውታል።

የክልሉ ህዝብ መከራ ግን በእዚህ አላበቃም ጉዳያችን በክልሉ ከሚገኙ ሦስት ከተሞች ለማጣራት እንደሞከረችው በአማራ ክልሎች ውስጥ የሚኖረው ህዝብ በቀትር ፀሐይ በሚዘርፉ ሌቦች ችግር ላይ ነው።''ቀን በቀን ይዘርፉሃል።'' አለ አንድ በአማራ ክልል ደቡብ ጎንደር ደብረታቦር ነዋሪ የሆነ ወጣት ለጉዳያችን አሁን ያለውን ሁኔታ ሲናገር።'' መንገድ ላይ ጩቤ አውጥቶ ሞባይል ይሁን ምንም የያዝከውን ይዘርፍሃል።'' በማለት ቃሉን ሰጥቷል። ወጣቱ ማን እንደሚዘርፍ ሲጠየቅ ''ማን እንደሆኑ አይታወቅም። ዝርፍያው በምሽትም ነው።አጋጣሚውን ተጠቅሞ ለመክበር የሚፈልግ አለ።'' በማለት አብራርቷል።

በተመሳሳይ በምስራቅ ጎጃም ነዋሪ ከሆነ ወንድሙ ጋር የተገናኘ የጉዳያችን አንባቢ በከተማዋ ያለውን ሁኔታ ሲገልጽ ወጥተን መግባት ስጋት ሆኖብናል።ከየት እንደተተኮሰ በማታውቀው ጥይት የመሞት አደጋ በራችን ላይ ነው በማለት የነገረውንና ከወጣቱ አንደበት የሰማው ከፍተኛ የፍርሃት፣የተስፋ መቁረጥና የሃዘን ስሜት ባነጋገረው ወቅት እንደተረዳ ሲገልጽ። '' እኔ በባህር ማዶ እያለሁ።ከርሱ ጋር ባደረኩት ንግግር እስካሁን ያጋባብኝ የሃዘን ስሜት አልለቀቀኝም'' በማለት ነበር የገለጸው።

አሁን በአማራ ክልል ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለው የጦር ሜዳው ገባ ወጣ ዜና ነው እንጂ የህዝቡን እውነተኛ ሰቆቃ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ግብ ተብሎ በዩቱበርም በመንግስት ሚድያም አይነገርም። ይህ በራሱ የሚያም ትልቅ ስብራት ነው።በአማራ ክልል ውስጥ ያለው ህዝብ ከረሃብ ጀምሮ እስከ ከፍተኛ የሃብት ውድመት እና ስነልቦናዊ ጥቃት ደርሶበታል።መንግስት በሚጠራቸው ስብሰባዎች ላይ የተለየ ሃሳብ ቢናገር ከታጣቂዎቹ ደጋፊዎችም ሆነ ከመንግስት ካድሬ ነገ እንዲህ ሊያደርጉኝ ይችላሉ በሚል ተሳቆ እውነቱን ለመናገር ተቸግሯል።

የክልሉ ህዝብ አሁን የናፈቀው ሰላም መቼ ነው የሚመጣው የሚለውን ጥያቄ የሚመልስለት ነው።ጉዳያችን ያነጋገረችው የደቡብ ጎንደር ነዋሪም ስራ ሁሉ መቆሙን ህዝብ ያለበትን የፈተና ደረጃ ከገለጸ በኋላ ችግሩ የሚፈታበት መንገድ እንዳይመጣ አንዱ ሽማግሌ ሃሳብ ቢያነሳ የመንግስት ደጋፊ ፋኖ ስለሆንክ ነው ይሉታል፣ ስለሰላማዊ ሃሳብ የሚያነሳ ሲሆን ደግሞ የብልጽግና ካድሬ ነህ ይሉታል።ስለሆነም የችግሩ ስፋት እንዲህ ቀላል አይደለም።በማለት አብራርቷል።በምስራቅ ጎጃም ነዋሪን ያነጋገረው የጉዳያችን አንባቢም ተመሳሳይ ሃሳብ አግኝቷል።በምስራቅ ጎጃም ነዋሪ የሆነው የክልሉ ነዋሪ ከሁሉም ያናደደው በክልሉ ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለው ችግር በውጭ ያሉ ዩቱበሮች እንደማይናገሩ መስማቱን ነበር። ኢንተርኔት ከመጥፋቱ በፊትም ሆነ አሁን በሚሰራበት መስርያቤት አልፎ አልፎ በሚለቀቀው የኢንተርኔት መስመሮች በውጭ የሚኖሩ ዩቱበሮች ስለ ታጣቂዎቹ እንጂ በህዝቡ ላይ እየደረሰ ስላለው መከራ አንዳች አለማውራታቸው በስማችን የሚነግዱ ለመሆናቸው ማስረጃ ነው በማለት በብሽቀት ገልጾለታል።

አንዳንዶች ይህ ተራ የስም ማጥፋት ወይንም የዩቱበሮቹን አመለካከት ለመጻረር የቀረበ ሊመስለው ይችል ይሆናል።ነገ ህዝቡ የሚናገረው እውነት ይሄው እንደሚሆን ጊዜ ያሳየናል።በክልሉ እየሆነ ያለው ብዙ ያልተነገረ ጉዳይ አለ።ከዘረፋው ወደትምህርት ቤት መሄድ ካልቻለው በላይ በክልሉ ከአስር ሺህ በላይ ቀዶ ጥገና ቀጠሮ ያላቸው የክልሉ ነዋሪ ህሙማን በጊዜ ቀዶ ጥገና ማድረግ ባለመቻላቸው ህይወታቸው አደጋ ላይ መሆኑን የራሱ የክልሉ ሚድያ የዘገበው ነው።ችግሩ የትዬለሌ ነው።ይህንኑ ግን የሚነግረን ሚድያ የለም።

መከላከያ ክልሉን ለቆ ይውጣ የሚለው  አባባል የአማራ ክልል ጥያቄ ነው?

''መከላከያ ክልሉን ለቆ ይውጣ'' የሚለው አባባል በመጀመርያ ህወሃት በትግራይ ሲያቀነቅነው ነበር። ዛሬ ላይ ደግሞ ሸኔ ይህንኑ በኦሮምያ እንዲደረግ ሲጠይቅ ተሰምቷል። ይህንን ጥያቄ የአማራ ክልል ህዝብ እንደጠየቀ ተደርጎ በአንዳንድ ዩቱበሮች ሲነገር መስማት ደግሞ የቅርቡ ክስተት ነው።የአማራ ክልል ህዝብ ከመከላከያው መሃል ህዝብ የበደሉ ለፍርድ ይቅረቡ ይላል እንጂ መከላከያ ክልሉን ለቆ ወጥቶ የመንግስት መዋቅር ለቆ እንዲወጣ አይፈልግም።መከላከያ አንድ ክልል ለቆ ወጣ ማለት ትርጉሙ ምን ማለት ነው? ይህንን ተከትሎ በአንድ ሀገር ውስጥ የሚኖር ክልል ምን ሊገጥመው ይችላል? አሁን ከደረሰበት ፈተና መልኩን ቀይሮ በምን ዓይነት የከፋ ችግር ላይ እንደሚወድቅ ለመተንበይ ሊቅ መሆን አይጠይቅም። ዛሬም ግን በአዲስ አበባ ሰላማዊ ሰልፍ በሚጠይቁ ሳይቀር መከላከያ ከ''ክልሉ ይውጣ'' ንግግር ሲነገር እየሰማን ነው።መከላከያ ከክልሎች ለቆ ይውጣ በራሴ ታጣቂ እተዳደራለሁ ማለት ሌላ ምንም ትርጉም ያለው ሳይሆን ኢትዮጵያ ትፍረስ፣በእየጎጣችን እንግባ የማለት ያህል ነው። አንዳንዶች ይህ ሲነገር ጉዳዩን ከጦርነቱ ጋር አያይዘው ብዙ ጉዳዮች ሊያነሱ ይችላሉ። ይህ መከላከያ ለቆ ይውጣ የሚለው አባባል ሶርያዎችም፣ሊብያዎችም ሆኑ የመኖች ከመፍረሳቸው በፊት የነበረ ዜማ ነው። አንዳንዴ አጀንዳዎቹን እነማን ከየት ቀድተው እንደሚያቀብሉን እየተረዳን ያለን አንመስልም።

ለማጠቃለል የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከሌላው ዓለም የተለየ ችግር አልገጠመውም።መፍትሄ የሌለው ችግርም የለም። የችግሮቻችን መነሻ ምክንያቶች በዛሬዋ ቀን ወይንም ምሽት የተፈጠሩባት አይደሉም።የረጅም ጊዜ የከመርናቸው የተሳሳቱ ትርክቶች፣የውስጥ ሴራዎች እና የባዕዳን እጅ ጭምር ናቸው። በእዚህ ጹሑፍ መነሻ ላይ በተያያዘው ሊንክ ላይ እንደተገለጸው በአማራ ክልል ላለው ችግር መነሻው በኦሮምያ ክልል የተነሳው የጽንፍ ኃይልና ይሄው ኃይል ደግሞ በመንግስት መዋቅር ውስጥ እንደፈለገ መስራቱ እንደሆነ ተብራርቷል።ወደመፍትሄው ለመምጣት ግን አሁንም ከእዚህ በፊት የክልሉ ግጭት ሲጀምር በነሐሴ ወር በጉዳያችን ላይ ቢወሰዱ ያልኳቸው የመፍትሄ ሃሳቦች አሁንም ዳግም ቢታዩ በማለት ይህንን የጉዳያችን ምጥን እቋጫለሁ።የመፍትሄ ሃሳቡ ሊንክ ''በአማራ ክልል የተነሳው አለመረጋጋትን በፍትሐዊ እና ርቱዕ በሆነ መንገድ ለመፍታት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ማድረግ የሚገባቸው ሦስት ተግባራት።'' በሚል ርዕስ የጻፍኩትን ሳላስታውስ አላልፍም።

==================//////==========

Sunday, November 26, 2023

በውግዘት ውስጥ ላሉት፣አሁንም በድፍረት ለሚሄዱት ለትግራይ የቀድሞ ጳጳሳት አልቅሱላቸው።


  •  አክሱም ጽዮን በክርስትና ታሪክ ለሁለት ሺህ ዓመታት ያህል ያላየችውን የድፍረት ስራ በቅዱስ ሲኖዶስ በተወገዙት የትግራይ አባቶች እያየች ነው።
  • የእነርሱን አካሄድ እየተመለከተ ዝም ብሎ የሚገለገለው የትግራይ ምዕመን፣ የእዚህ ዓይነት አካሄድ ከአባቶቻችን አልተማርንም ተዉ! ማለት ይገባዋል።

እራሳቸውን ከቅዱስ ሲኖዶስ ለይተው፣ክርስትናን በመንደር ለመመተር የሚሞክሩት የትግራይ አባቶች ከቅዱስ ሲኖዶስ ውግዘት እና ስልጣነ ክህነት መያዝ በኋላም አባ ሰረቀን ጵጵስና ሾመናል ብለዋል። ይህ የድፍረት ስራ አክሱም ጽዮን በክርስትና ታሪክ  ለሁለት ሺህ ዓመታት ያህል ያላየችውን የድፍረት ስራ በትግራይ አባቶች እያየች ነው።

ይህ በትግራይ ያሉ አባቶች እያደረጉት ላለው አዕምሮውን የሳተ ሰው ስራ ምንም ሃተታ አያስፈልገውም።ድርጊቱ ስንት የበቁ አባቶች ዘግተው ቀን ከሌሊት ለዓለም የሚጸልዩ አባቶች ባሉባት የትግራይ ክልል እና በአክሱም ጽዮን ፊት የተፈጸመ ድፍረት ነው።ጥፋት በበለጠ ጥፋት አይስተካከልም።በውግዘት ውስጥ ላሉት፣አሁንም በድፍረት ለሚሄዱት ለትግራይ የቀድሞ ጳጳሳት አልቅሱላቸው።አሁን ለአባቶች የሚያስፈልጋቸው ለቅሶ ነው።ከልቦናቸው አይደሉም።ከልቦናው የሆነ አባት ቅዱስ ፓትርያሪክ በብዙ ድካም ከደጁ ሲመጣ የቤተክርስቲያን ደጅ ዘግቶ አይሸሸግም፣ቡራኬ ሊቀበል እየተጣደፈ ሄዶ ጉልበት ስሞ ይባረካል።

አሁን የትግራይ አባቶች ከቀልባቸው አይደሉም።ምን እያደረጉ እንደሆነ፣ምን እየሰሩ እንደሆነ ከአዕምሯቸው ጋር ስላልሆኑ አያውቁትም። አሁን የሚያስፈልጋቸው የሚያደርጉትን አያውቁምና የሚያለቅስላቸው፣ ወደ ቀልባቸው መልሳቸው ብሎ የሚያነባላቸው ሰው ያስፈልጋቸዋል። የእነርሱን አካሄድ እየተመለከተ ዝም ብሎ የሚመለከተው የትግራይ ምዕመንስ? ቢያንስ የእዚህ ዓይነት አካሄድ ከአባቶቻችን አልተማርንም አይልም? በመንደር ተሰባስቦ ከቅዱስ ሲኖዶስ አንድነት ወጥቶ እንደፈለጉ በመሄድ የሚሰጥ ስልጣነ ክህነትን የትግራይ ምዕመናን ከአባቶቻችን አልተማርነውም።ከየት አመጣችሁት ብሎ አይጠይቅም? 



Saturday, November 25, 2023

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።